የዋና ሥራ አስፈጻሚ መልዕክት
የተከበራችሁ የባንካችን ባለአክሲዮኖች፣
በመጀመሪያ ሁላችሁንም ከልብ በመነጨ ሰላምታ ሰላም ማለት እወዳለሁ፡፡
ዓለማችን ካለፈው ዓመት ዘገምተኛ የኢኮኖሚ ዕድገት ማገገሟን ተከትሎ የተለያየ መጠንና ደረጃ ያላቸው ተግዳሮቶች እያስተናገደች ቀጣይና ተከታታይ እድገት እና የኢኮኖሚ ማገገም ማስመዝገብ ተቸግራ ትታያለች፡፡ በዓለምአቀፉ ማኅበረሰብ የተቀናጀ ጥረት እና ፈጣን የኮቪድ ክትባት እንዲሁም የህክምና መሳሪያ ስርጭት ምክንያት የወረርሽኙ አደጋ የተገደበ ቢሆንም የማኅበረሰብ ቀውስ በማስከተል፣ ሥራን በማወክና እድገትን በመገደብ በሽታው ከፍተኛ አሉታዊ ተጽዕኖ አሳድሯል፡፡ የ2022 ዓመታዊው የዕድገት ምጣኔ ትንበያም በዋናነት በግዙፎቹ የቻይና እና የአሜሪካ ኢኮኖሚ ከሚጠበቀው መቀዛቀዝ ጋር ተያይዞ ወደ 4.4% ዝቅ በማለት ቅናሽ የተመዘገበበት ነው፡፡ በ2022 መባቻ ላይ የተቀሰቀሰው የራሺያ-ዩክሬይን ጦርነት እየዳኸ ለነበረው የአለማቀፉ ኢኮኖሚ መልካም ዜና አልነበረም፡፡ የጥቁሩ-ባሕር ሀገራት በስንዴ እና ቅባት እህሎች ምርት ላይ ካላቸው ትልቅ የምርታማነት ድርሻ ጋር በተያያዘ በምግብ እና ሸቀጦች ዋጋ ማሻቀብ ሳቢያ የግጭቱ መከሰት አሉታዊ ገጽታዎች ለመታየት ጊዜ አልፈጀባቸውም፡፡
እየጨመረ ያለው እና አብዛኛውን ዓመት በሁለት-አኃዝ ሲጓዝ የነበረው የዋጋ ንረት እንዲሁም የሰሜኑ ጦርነት የተለያዩ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ቀውሶች ያስከተሉ ሁለት በሀገራችን የተከሰቱ ታላላቅ ተግዳሮቶች ነበሩ፡፡ በግብርናው ዘርፍ እየታዩ ያሉ በርካታ ተስፋ ሰጪ እንቅስቃሴዎች መንግስት የዋጋ ንረትን ለመቆጣጠር እየወሰዳቸው ያሉትን ስትራቴጂያዊ እርምጃዎች ማሳያ እንደሆኑ ማየት ይቻላል፡፡
በርካታ አዳዲስ ባንኮች የባንክ ኢንደስትሪውን ከመቀላቀላቸው ጋር ተያይዞ ዘርፉ በመስፋት ላይ ይገኛል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ከተለመዱት የባንክ ተቋማት ባሻገርም ኢትዮ-ቴሌኮም እና በርካታ የፋይናንስ-ቴክኖሎጂ ኩባንያዎች ዘርፉን በመቀላቀል ላይ ይገኛሉ፡፡ ዘርፉን ለውጭ የፋይናንስ ተቋማት ክፍት ለማድረግ ከሚደረገው የመንግስት ጥረት ጋር ተያይዞ ውድድሩ የበለጠ እየጠነከረ እንደሚሄድ ይጠበቃል፡፡ በዓመቱ ከታዩ ሌሎች ተጠቃሽ የመንግስት እንቅስቃሴዎች መካከል በሀገራችን የአክሲዮን ገበያ እንዲቋቋም የአክሲዮን ገበያ አዋጅን ከማስጸደቅ አንስቶ የኢትዮጵያ የሰነደ-ሙዓለ ንዋያት ገበያን እስከ መመስረት ድረስ በመንግስት የተከናወነው ስራ ዋነኛው ነው፡፡
በሪፖርት ዓመቱ፣ ከበርካታ የታቀዱ ስራዎች አንጻር በሁሉም በሚባል ደረጃ ዓላማችንን አሳክተናል፡፡ ተደራሽነታችንን በማስፋት እንዲሁም በበርካታ የሕንጻ ግንባታ ፕሮጀክቶች ላይ ኢንቨስት በማድረግ አጠቃላይ የስራ እንቅስቃሴያችንን ለማሳደግ ጥረት አድርገናል፡ ፡ በዓመቱ ባደረግነው የቅርንጫፍ ማስፋፋት ስራ ጠቅላላ የባንካችንን ቅርንጫፎች ብዛት
ወደ 373 በማሳደጋችን የደንበኞቻችንን ብዛት ወደ 1.7 ሚሊዮን እንድናደርስ ረድቶናል፡፡ ይህም በሁለቱም ቁልፍ ተግባራት የ30% እና 39.2% በመቶ ዓመታዊ እድገት የተመዘገበበት ነበር፡፡ የባለፈውን ዓመት አመርቂ ውጤት ተከትሎ የባንካችንን የተቀማጭ ገንዘብ መጠን በ35 በመቶ በማሳደግ መልካም የሚባል ውጤት ተመዝግቧል፡፡ በሰሜኑ የሀገራችን ክፍል በነበረው ግጭት ሳቢያ በርካታ ቅርንጫፎቻችን ስራ ለማቆም መገደዳቸው የሚያስቆጭ አጋጣሚ ሆኖ አልፏል፡፡ ይሁንና እነዚህ ቅርንጫፎች ከደረሰባቸው ጥፋት በሚቻለው ፍጥነት አገግመው ወደነበሩበት በመመለስ ስራ ለማስጀመር ያደረግነው ጥረት የተሳካ ነበር፡ ፡ በተግዳሮቶች የታጀበ ዓመት ብናሳልፍም የበጀት ዓመቱ ውጤቶቻችን መልካም የሚባሉ በመሆናቸው በተለይም ጠቅላላ ገቢያችንን የ30% ጭማሪ በማሳየት ወደ ብር 4.4 ቢሊዮን ከፍ በማድረጋችን ዓመታዊ ትርፋችንን በ13% ማሳደግ ችለናል፡፡
ባንካችን የማኅበራዊ ኃላፍነቱን ከመወጣት አንጻርም ከፍ ያለ መዋዕለ-ነዋይ በመመደብ ለተለያዩ የኅብረተሰብ ክፍሎች ድጋፍ አድርጓል፡፡ በተጨማሪም ከባንካችን ለጋስ እጆች ባሻገር ሰራተኞቻችንም በጦርነቱ ምክንያት ለተፈናቀሉ ወገኖች ድጋፍ የሚውል ሰብዓዊ ዕርዳታ በማሰባሰብ ልገሳ አድርገዋል፡፡
በዘርፉ አጠቃላይ ከባቢ ውስጥ የነባራዊ ችግሮችንና ተጠባቂ መሰናክሎች ላይ የጠራ እይታ በመያዝ፣ በመጪዎቹ ዓመታት የማይናወጥ ቀጣይነት የሚኖረው እድገት መቀየስ ቀዳሚ ተግባራችን ይሆናል፡፡ የውድድር ዓለሙን በአስተማማኝ ሁኔታ ሊያሻግር የሚችል የስኬት ጎዳና ለመቀየስ የሚያስችለንን አዲስ የአምስት ዓመት መሪ-ዕቅድ ዝግጅት ፕሮጀክት በይፋ ለመጀመር ሙሉ ዝግጅታችንን አጠናቀናል፡፡ ከዚህ ጎን ለጎን ሙሉ ትኩረት በሚሰጠው ደረጃ የተሻለ አሰራር እና የደምበኞች አገልግሎት በማቅረብ ስራችንን ይበልጥ ለማሳደግ እንተጋለን፡፡
በበጀት ዓመቱ የገጠሙንን ችግሮችና ተግዳሮቶች ተቋቁመን ውጤታማ እንድንሆን የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክን ጨምሮ ሁሉም ባለድርሻ አካላት የማይተካ ሚና ተጫውተዋል፡፡ ድጋፋቸውና እጅግ ጠቃሚ ምክራቸው ዓመቱን ሙሉ ያልተለየን የባንካችን የዳይሬክተሮች ቦርድ አባላትን በተለየ ሁኔታ ማመስገን እንወዳለን፡፡ ለውድ ደንበኞቻችንም ልባዊ ምስጋናችንን እያቀረብን የተሻለ ልናገለግላቸው ቃል እንገባለን፡፡
አመሰግናለሁ!
የኋላ ገሠሠ
ዋና ሥራ አስፈጻሚ